ዜና
የሀገር ውስጥ
የቴክኒክና ሙያ ትምህርት (TVET) ተመዝጋቢዎች ከ50 በመቶ በላይ መቀነሱና በኢንዱስትሪ እድገት ላይ ስጋት መፍጠሩ ተገለፀ
on | 2026-02-23 08:32:43 on2026-03-01 14:09:23
Share: Facebook |
Twitter |
Whatsapp |
Linkedin
አዲስ አበባ — በኢትዮጵያ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት (TVET) ተቋማት የተመዝጋቢ ተማሪዎች ቁጥር በቅርብ ሶስት ዓመታት ውስጥ ከ50 በመቶ በላይ መቀነሱ አዲስ ጥናት አረጋግጧል።
ይህ መቀነስ ሀገሪቱ ወጣቶችን በኢንዱስትሪ ችሎታ ለማበረታታት በምትጥርበት ወቅት መከሰቱ ጥልቅ ስጋት አስነስቷል።
በየስ ፓክት (YES-PACT) ኢኒሺዬቲቭ አካል የተዘጋጀው የTVET የአገር ጥናት ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ ተመዝጋቢዎች ቁጥር በ2020/21 ዓ.ም 478,910 ከነበረ በ2023/24 ዓ.ም ወደ 213,663 ዝቅ ብሏል። ጥናቱ በAfrican Center for Economic Transformation (ACET) እና በPolicy Studies Institute (PSI) በመተባበር ተዘጋጅቶ የካቲት 12 ቀን 2026 ይፋ ተደርጓል።
የጥናቱ ዋና ውጤቶችን ያቀረቡት በACET የፆታ እኩልነት ፕሮግራም ኃላፊ አዳምነሽ ቦጋለ እንደገለጹት፣ ዋናው ምክንያት የትምህርት ፖሊሲ መዋቅራዊ ለውጥ ነው። ቀድሞ ከ10ኛ ክፍል የጨረሱ ተማሪዎች ወደ TVET መግባት ይችሉ ነበር፤ አሁን ግን 12ኛ ክፍል ማጠናቀቅ የመግቢያ መስፈርት ሆኗል። ይህ የተማሪዎችን መሠረታዊ እውቀት ለማጠናከር ቢታሰብም፣ በአጭር ጊዜ የተመዝጋቢ ክፍተት ፈጥሯል ተብሏል።
ከፖሊሲ ለውጥ በተጨማሪ፣ TVET በማብበረሰቡ ዘንድ እንደ “ሁለተኛ ምርጫ” የሚቆጠር እና ይህ አመለካከት የሙያ ትምህርትን እንደ ዩኒቨርሲቲ መግባት ያልቻሉ ብቻ የሚመርጡት አማራጭ ተደርጎ እንደሚታሰብ ተገልጿል።
በPSI የIUPRC ኃላፊና አስፈጻሚ ተመራማሪ አማረ ማተቡ እንደገለጹት፣ የኢኮኖሚ እድገት በገበያ ፍላጎት የተመሠረተ የስልጠና ስርአት በመገንባት ብቻ ሊረጋገጥ ይችላል። ጥናቶች በወረቀት ላይ ብቻ እንዳይቀሩ ወደ ተግባር መቀየር እንዳለባቸውም ጠቁመዋል።
ጥናቱ የሚጠቅሳቸው ዋና እንቅፋቶች አምስት ናቸው፤ የኢንዱስትሪ ልምድ ያላቸው አስተማሪዎች እጥረት፣ የተሻሻለ መሣሪያ እና መሠረተ ልማት እጥረት፣ የግል ዘርፍ የተስተካከለ ተሳትፎ አለመኖር፣ የከፍተኛ ወጪ ፕሮግራሞች የፋይናንስ እጥረት፣ እና የዲጂታል ክህሎቶች—በተለይም የአርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ (AI)—በካሪኩላም ውስጥ አለመካተት ናቸው።
ሀገሪቱ ወደ አራተኛው የኢንዱስትሪ አብዮት እያመራች ባለችበት ወቅት የTVET ካሪኩላም በስፋት እንዲዘመን ጥሪ ቀርቧል። በአግሮ-ፕሮሰሲንግ፣ በኮንስትራክሽን፣ በማኑፋክቸሪንግ እና በቴክኖሎጂ የተደገፉ አገልግሎቶች ላይ የሚታዩ ዕድገቶች እንደ ቅድሚያ ዘርፎች ተጠቅሰዋል።
መንግስት እንደ አመቻችና ተዋናይ ሚና እንዲወስድ እና የግሉ ዘርፍ የሰው ኃይል አቅርቦትን በማቅረብ እንዲሳተፍ ተጠይቋል። አሁን ያለው ጊዜ ዘርፉን እንደገና ለመቅረጽ ወሳኝ መሆኑን ሪፖርቱ ጠቁሟል።